የሳንኩራ ወረዳ አስተዳደር በስልጤ ዞን ከሚገኙ 10 ወረዳዎችና 05 ከተማ አስተዳደሮች ውስጥ አነዷ ስትሆን ወረዳዋ በለውጥ ጎዳና ውስጥ ከሚገኙ የዞኑ ወረዳዎች አንዷ ናት፡፡ ወረዳዋ ዋና መቀመጫ ዓለም ገበያ ከተማ ሲሆን ከዞኑ ዋና ከተማ ወራቤ በስተ ደቡብ አቅጣጫ 40 ኪሎሜትር ርቀት ከማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንግስት ርዕሰ ከተማ ሆሳዕና በስተ ምስራቅ አቅጣጫ 70.ኪ.ሜ እና ከሀገራችን ርዕሳ ከተማ አዲስ አበባ በስተደቡብ አቅጣጫ 212 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ትገኛለች፡፡Read More
የሳንኩራ ወረዳ በ26 ቀበሌዎችና በአንድ ታዳጊ ማዘጋጃ ቤት ከተማ የተዋቀረች ሲሆን በወረዳዋ ከ1መቶ 4ሺ በላይ የሚጠጋ የህዝብ ብዛት አለት። በወረዳው የሚገኘው አብዛኛው የማህበረሰብ ክፍል የእስልምና እምነት ተከታይ ሲሆን የስልጥኛ ቋንቋ ተናጋሪ ነው። በወረዳው የሚገኘው ማህበረሰብ አብዛኛው የእስልምና እምነት ተከታይ ይሁን እንጂ የተለያየ ብሔርና ሃይማኖት ያላቸው ተከታዮች በሰላምና በፍቅር ተዋደውና ተከባብረው በጋራ የሚኖሩባት ፤ የአብሮነትና የአንድነት መገለጫ የሆነች ወረዳ ነች፡፡
በተለይም ወረዳዋን አቋርጦ የሚያልፈው ሀገር አቋራጭ የአስፓልት መንገድ ተጠቃሚ መሆን መጀመር በወረዳዋ መጀመሪያውኑ የነበረውን ለኑሮ ፣ ለንግድና ኢንቨስትመንት ምቹና በባህሪው ሞቅ ያለ የህዝብና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ወደ ላቀ ደረጃ እንዲሸጋገር ምቹ ሁኔታን የፈጠረ ሲሆን ይህም ወረዳዋ በሁሉም ዘርፍ ፈጣንና አስተማማኝ መዋቅራዊ ኢኮነሚያዊ ዕድገት እያስመዘገበች በፈጣን ዕድገት መገስገስ እንድትችል ትልቅ አቀም መፍጠር ችሏል፡፡
እጅግ በጣም ልማታዊ አስተሳሰብና ጠንካራ የማህበራዊ ትስስር መስተጋብር ያለው ድንቅ ህዝብ ባለቤት የሆነችው የሳንኩራ ወረዳ ፤ ስራ ወዳድና ለወረዳው ልማትና ዕድገት የጀርባ አጥንት በሆነው ህዝቧ ቁርጠኝነት በማህበራዊ ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ዘርፎች በተሰሩ ስራዎች የተገኘው ውጤት ፤ ወረዳዋን በአዲስ የዕድገት ገፅታ በመለወጥ የብዙዎችን ቀልብ መሳብ እንድትችል አስችሏታል፡፡
ጤናማ ማህበረሰብ ለአንድ ሀገር እድገት የሚያበረክተው አስተዋጽኦ የጎላ መሆኑን ተከተሎ የወረዳውን ማህበረሰብ ጤና በተገቢው ለማስጠበቅ ሁለት ጤና ጣቢያዎች እንዲሁም 26 ጤና ኬላዎች ተገንብተው ለህብረተሰቡ በቅርበት የህክምና አገልግሎት እየሰጡ ይገኛል፡፡
የተማረና የሰለጠነ የሰው ሀይል በብዛትና በጥራት በማፍራት በሀገራችን ብሎም በወረዳው የተጀመረውን የእድገትና የብልጽግና ጉዞ ከዳር ለማድረስ ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ ሲሆን 02 ሁለተኛ ደረጃና የመሰናዶ ትምህርት ቤቶች 29 የአንደኛና መካከለኛ ደረጃ እንዲሁም 54 የቅድመ-አንደኛ ትምህርት ቤቶች ፤ ተገንብተው ሙሉበሙሉ ወደ መማር ማስተማር ሥራ ገብተው ትውልድ የመቅረፅና የተማረና የሰለጠነ ትውልድ ለመፍጠር የበኩላቸውን በማበርከት ላይ ይገኛሉ፡፡
የሳንኩራ ወረዳ ማህበረሰብ አብዛኛው አርሶ አደርና በእርሻ ስራ የሚተዳደር እንደ መሆኑ መጠን ያመረተውን ምርት በወቅቱ ለገበያ ማቅረብ እንዲችል ፤ ምቹ የሆነ የመንገድ ዝርጋታ አስፈላጊ ሲሆን አሁን ላይ በአብዛኛው ቀበሌዎች ምቹ የዩራፕ መንገድ ዝርጋታ አገልግሎት እየሰጠ ሲሆን የወረዳውን ማህበረሰብ በማስተባበር ወረዳው ግሬደርና ሎደሮችን በመግዛት ፤ ቀበሌዎችን ከዋናው አስፓልት እና ቀበሌዎችን ከቀበሌዎች እንዲሁም መንደሮችን ከመንደሮች ማገናኘት የሚያስችሉ የጥርጊያ መንገድ ስራዎች ተሰርተው ማህበረሰቡ በቀላሉ ያመረተውን ምርት ለገበያ ማቅረብ እንዲችል እየተደረገ ይገኛል፡፡
በሌላም በኩል በንፁህ መጠጥ ውሃ አቀርቦት ረገድ የሚስተዋሉ ችግሮችን ከዞን ከክልልና ከፌዴራል መንግስት ጋር በመሆን የተለያዩ የማስፋፊያ ስራዎች እየተከናወኑ ሲሆን የግንባታ ስራዎቹ ተጠናቀው አገልግሎት መስጠት ሲጀምር ሙሉ ለሙሉ በወረዳው ያለውን የውሃ አቅርቦት ተደራሽነት ችግር የሚቀርፍ ሲሆን በቴሌኮሙኒኬሽንና በመብራት ዝርጋታ ለወረዳው ማህበረሰብ ያልተቋረጠ አገልግሎት እየሰጡ የሚገኝበት ምቹ ሁኔታም ተፈጥሯል ፡፡
የሳንኩራ ወረዳ ምቹ የስህነ ምዳር መሬት ባለቤት መሆኗን ተከትሎ ሰብል አብቃይ ከሆኑ የዞኑ መዋቅሮች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት የምትጠቀስ ሲሆን በዋናት በወረዳዋ በቋሚነት በቆሎ ፣ ስንዴ ፣ ጤፍ በርበሬ ፣ ዳጉሳና ማሽላ በስፋት በየዓመቱ የሚለማ ሲሆን በዘመናዊና የጉድጓድ ውሃን በመጠቀም በ5 ቀበሌዎች ላይ በመደበኛና በበጋ መስኖ በስፋት የሚለማበት ምቹ ሁኔታ ያላት ወረዳም ጭምር ነች፡፡
ወረዳዋ በብዛት ተፈላጊ የሆኑ የካሽ ክሮፖቹ ተመርተው ለገበያ የሚቀርቡባት አንደመሆኗ መጠን የሀገራችን መንግስት ለግብርናው ዘርፍ የሰጠውን ልዩ ትኩረት ከግምት በማስገባት እንደ ወረዳ የዘርፉን ውጤታማነት ለማሳደግ በተሰራው ስራ በየዓመቱ የምርትና ምርታማነት ዕድገት መጨመር እንዲችል ማስቻሉን ተከትሎ በርካታ ቁጥር ያላቸው የወረዳው አርሶ አደሮች ኢኮነሚያዊ አቅማቸው እንዲጨምር ከማስቻሉም በላይ በተለያዩ የአገልግሎት ዘርፎች ላይ መሰማራት የሚያስችል መዋዕለ ነዋያቸውን በማፍሰስ ወደ ኢንቨስተርነት መሸጋገር እንዲችሉ ትልቅ አቅም የፈጠረ ዘርፍ ሆኗል፡፡
ተፈጥሮን ያለስስት የተለገሰው የሳንኩራ ወረዳ በስፋት የለሙ የኢንቨስትመንት መሬቶች መኖሩን ተከትሎም በርካታ ባለሀብቶች ወረዳዋን መርጠው በግብርናና በአገልግሎት ዘርፍ ኢንቨስት በማድረግ ለወረዳው እና ለሀገር ልማት እድገት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እያበረከቱ ይገኛል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም የሳንኩራ ወረዳ ሌላው ተመራጭ ከሚያደርጓት ገጽታዎቿ አንዱ የባህልና የቱሪስት መዳረሻነቷ ሲሆን በዋናነት በዞኑ ከተመዘገቡ የቱሪስት መስህቦች መካከል ጥቅጥቁ የሀንዶሼ ደን ተጠቃሽ ሲሆኑ እኚህ መዳረሻዎች የወረዳው ሌላኛው ገጽታ በመሆን ተጨማሪ ውብትን የሚያጎናጽፉ ተፈጥሯዊ ሀብቶች ናቸው፡፡
በዚህም መሰረት ዛሬ ላይ ቆሞ በጊዜ መነፅር የኋሊት አሻግሮ ወረዳዋን መመልከት ለቻለ በፈጣን የእድገት ጉዞ እየገሰገሰች ስለመሆኗ ለመመስከር ነጋሪ የሚያሻው ባለመሆኑ ወረዳዋ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያስመዘገበች ያለው ፈጣን እድገትም አሁን ያለችበትን መልክ እንድትይዝ ትልቅ አቅም መፍጠር ችሏል፡፡
በመሆኑም በወረዳዋ በሁሉም ዘርፍ የተጀመረውን የልማትና የለውጥ እንቅስቃሴ ወደ ላቀ ምዕራፍ ለማሸጋገር የወረዳው መንግስት ከወረዳው ህዝብ ጋር እጅ ለእጅ ተያይዞ ለተሻለ ለውጥና የዕድገት ጉዞ እየተጋ ይገኛል፡፡
በመጨረሻም የሳንኩራ ወረዳ አስተዳደር ፤ በወረዳው ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በአገልግሎትና በንግድ እንዲሁም በሌሎች የኢንቨስትመንት ዘርፎች በመሰማራት ከራሳቸው አልፎ ለወረዳው ዕድገት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ማበርከት ለሚፈልጉ ልማታዊ ባለሀብቶች ፤ክፍት የከተማ መሬቶችን ያዘጋጀ ሲሆን ይህን ምቹ ሁኔታ ተቀብሎ ወረዳዋን ለማልማት የሚመጣን ባለሀብት ፤ የወረዳው አስተዳደር “አርሂቡ የምጣቢኝ” በማለት ተቀብሎ በልዩ መስተንግዶ ለማስተናገድ ዝግጁ መሆኑን ለመግለፅ ይወዳል፡፡